የዩኒቨርሲቲው ኢንደስትሪ ትስስርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክቶሬት በደ/ብ/ብ/ሕ/ክ/መንግስት መገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ የኢኮቴ ግ/ሥ/ፈ/ማ/አገ/አስ/ዳይሬክቶሬት ጋር በመተባበር በዩኒቨርሲቲው ውስጥ ለተደራጁ ኢንኩቤቲዎች በሶፍት ዌር ልማት፣ በኔትወርኪንግ፣ በኮምፒውተርና ቢሮ ማሽን ጥገና፣ በቢዝነስ ዕቅድ አዘገጃጀት እና በኢንተርፕሪነርሽፕ ዙሪያ ከጥቅምት 29 እስከ ኅዳር 9/2010 ዓ.ም ለተከታታይ 10 ቀናት ስልጠና ሰጥቷል፡፡ ምስሎቹን ለማየት እዚህ ይጫኑ::

ስልጠናው 80 በመቶ በተግባር እንዲሁም 20 በመቶ በንድፈ ሀሣብ የተሰጠ ሲሆን የኔትዎርኪንግና አይሲቲ ዘርፍ ተግባራዊ ሥራዎችን እንዲመለከቱ የሚረዳና እና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳም የሚኖረው መሆኑን በክልሉ የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ የኔትወርኪንግ ባለሙያ አቶ ነጋሲ ቸሬ ተናግረዋል፡፡

ስልጠናው በ3 ዙሮች ለ2ኛና 3ኛ ዓመት የኤሌክትሪካል ኢንጂነሪንግ እና ኮምፒውተር ሣይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ተማሪዎች የተሰጠ ሲሆን ተማሪዎቹ በዩኒቨርሲቲው በሚኖራቸው ቆይታ ከሥልጠናው ጋር የተያያዙ ሥራዎችን እየሠሩ አቅማቸውን በማጎልበት የሚቆዩ ይሆናል፡፡ ሠልጣኞች በዩኒቨርሲቲው ውስጥም ሆነ በውጭ የሚፈጠሩ የሥራ ዕድሎችን በመጠቀም እንዲሁም በማኅበራት በመደራጀት ሥራ የሚፈጥሩበት ዕድል እንዲያመቻቹ የሚረዳ መሆኑን የዩኒቨርሲቲው ኢንደስትሪ ትስስርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክቶሬት ተወካይ አቶ ደሳለኝ ጃራ ገልፀዋል፡፡

ሰልጣኝ ተማሪ ካሊድ ጥላሁንና ተማሪ ዘሃራ ያሲን በሰጡት አስተያየት ከስልጠናው ብዙ የማያውቋቸውን ነገሮች ለማወቅ እንደቻሉና ለወደፊቱ በቡድንም ሆነ በግል በርካታ ሥራዎችን ለማከናወን መነሳሳታቸውን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም ዓላማና ግብ በመቅረፅ ተቀጣሪነትን ሳንጠብቅ ሥራ ፈጣሪ በመሆን ጥሩ ደረጃ ላይ ለመድረስና ለዩኒቨርሲቲውም ሆነ ለአካባቢው ማኅበረሰብ የበኩላችንን አስተዋፅዖ ለማበርከት ያስችለናል ብለዋል፡፡