7ኛው የመላው ደቡብ የውሃ ስፖርቶች ውድድር ከታህሳስ 18-23 ዓ/ም በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የመዋኛ ገንዳ ተካሂዷል፡፡

ከክልሉ የተለያዩ ዞኖች የተወጣጡት ተወዳዳሪዎች በዩኒቨርሲቲው መዋኛ ገንዳ ለሦስት ወራት ያህል ልምምድ ሲያደርጉ የቆዩ ሲሆን በዚህ ዓመት መቐለ ላይ በሚደረገው ሀገር አቀፍ ውድድር ደ/ብ/ብ/ህ ክልልን የሚወክሉ ይሆናሉ፡፡ምስሎቹን ለማየት እዚህ ይጫኑ::

የክልሉ ስፖርት ፌዴሬሽን ልምምዱንና ውድድሩን በአ/ም/ዩ የመዋኛ ገንዳ ለማድረግ ፈቃድ በጠየቀው መሰረት የተፈቀደለት መሆኑንና የማደርያ፣ የቁሳቁስ እና ሌሎች የቴክኒክ ድጋፎች ሲደረግላቸው መቆየቱን የዩኒቨርሲቲው ስፖርት አካዳሚ ዳይሬክተር ዶ/ር ቾምቤ አናጋው ገልጸዋል፡፡

ባለፈው አመት ሀዋሳ ከተማ ላይ በተደረገው ሀገር አቀፍ ውድድር ደ/ብ/ብ/ህ ክልል በሁለተኛነት ያጠናቀቀ ሲሆን ለውጤቱ ዩኒቨርሲቲው ያበረከተው አስተዋጽኦ ከፍተኛ በመሆኑ ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድርና ከክልሉ ስፖርት ፌዴሬሽን ምስጋና እንደተበረከተለት ዶ/ር ቾምቤ ተናግረዋል፡፡

የደ/ብ/ብ/ህ/ክ/መ የዋና ፌዴሬሽን ፕሬዝደንት አቶ ጳውሎስ ሙኔ እና የክልሉ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ም/ቢሮ ኃላፊና የስፖርት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ገልገሎ ገዛሃኝ ውድድሩን ሲያስጀምሩ ዩኒቨርሲቲው ላደረገላቸው ከፍተኛ ትብብር ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡