የሥነ-ትምህርት እና ሥነ-ባህርይ ሣይንስ ት/ቤት ለዩኒቨርሲቲው አዲስ ገቢና በተለያዩ ምክንያቶች ሥልጠናውን ላልወሰዱ ነባር መምህራን "Higher Diploma Program"(HDP) ሥልጠና ከኅዳር 12-/2009 ዓ.ም ጀምሮ በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ ምስሎቹን ለማየት እዚህ ይጫኑ::

የሥልጠናው ዓላማ የመምህራንን ማስተማር ክህሎት ይበልጥ ማሳደግና ማዳበር፣ በመማር ማስተማር ሂደት የሚፈጠሩ ክፍተቶችን በመሙላት የተቀላጠፈና ጥራቱን የጠበቀ ትምህርት እንዲሰጥ ማስቻል እና ችግር ፈቺ ምርምሮችን እንዲሠሩ ማብቃት መሆኑን በወቅቱ የሥልጠናው አስተባባሪ አቶ መስፍን ባልጉ ገልፀዋል፡፡

ሥልጠናው በዋናነት አሳታፊ የመማር ማስተማር ሂደትና የክፍል አያያዝ፣ ጥናትና ምርምሮችን በተቋማትና በትምህርት ቤቶች መተግበር እና በመማር ማስተማር ሂደት ሊያጋጥሙ የሚችሉ ችግሮችና የመፍትሔ አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ ሲሆን በአራት የሥልጠና ሞጁሎች ለ132 ሰዓታት የሚሰጥ ነው፡፡ ይህም በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ የሚጠናቀቅ መሆኑን አስተባባሪው ተናግረዋል፡፡

ሥልጠናው ቀደም ሲል በሙያዉ ላይ ለሚገኙ እንደማጠናከሪያ ሲያገለግል ለአዲስ ገቢ መምህራን የሙያ ክህሎትና ዕውቀት የሚጨብጡበትና በተግባር ለውጥ የሚያመጡበት እንደሚሆን ሠልጣኞች አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

ሥልጠናው በሥነ-ትምህርት እና ሥነ-ባህርይ ሣይንስ ት/ቤት መምህራን የሚሰጥ ሲሆን በሁሉም ካምፓሶች የሚገኙ 238 መምህራን በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ፡፡