የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ኅብረትና የሰላም ፎረም ከዩኒቨርሲቲው ጋር በመተባበር በ2014 ዓ/ም ወደ ዩኒቨርሲቲው ለተቀላቀሉ አዲስ ገቢ ተማሪዎች ከግንቦት 1-2 /2014 ዓ/ም አቀባበል አድርገዋል፡፡ፎቶዎቹን ለማየት እዚህ ይጫኑ

የተማሪዎች አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አየልኝ ጎታ እንደገለጹት በዘንድሮው የትምህርት ዓመት 4,994 ተማሪዎች የተመደቡ ሲሆን ዩኒቨርሲቲው ተማሪዎቹን ለመቀበል የመኝታ፣ የካፍቴሪያና የክሊኒክ አገልግሎት እና ሌሎችም ቅድመ ዝግጅቶችን አድርጓል፡፡

ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው በብሔር፣ በሃይማኖትና በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የተመሠረቱ ጥቃቶች፣ ፀብና ጥላቻን በመፀየፍ በትምህርታቸው ላይ ብቻ ትኩረት እንዲያደርጉና ዓለም አቀፋዊ ዕውቀትና መልካም አስተሳሰብ እንዲያዳብሩ ዳይሬክተሩ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የተማሪዎች ኅብረትና ሰላም ፎረም በጋራ አስተባባሪዎችን በመምረጥ ተማሪዎች ሳይቸገሩና ሳይጉላሉ ወደየተመደቡባቸው ካምፓሶች እንዲገቡ መጓጓዣ በማመቻቸት እየሠሩ መሆኑን የተማሪዎች ኅብረት ም/ፕሬዝደንት ተማሪ ምሕረት ተካልኝ ገልጻለች፡፡

ዩኒቨርሲቲው ሰላማዊና ለመማር ማስተማር ሥራ ምቹ በመሆኑ ተማሪዎች በምንም ዓይነት ሁኔታ ሳይረበሹ ለትምህርታቸው ትኩረት ሰጥተው በርትተው እንዲማሩ አሳስባለች፡፡

የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት