አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ሳውላ ካምፓስ በተለያዩ የትምህርት መስኮች ለ3ኛ ጊዜ ያሠለጠናቸውን 329 ተማሪዎች ጥር 20/2013 ዓ/ም በደማቅ ሁኔታ አስመርቋል፡፡ ከተመራቂዎቹ መካከል 111ዱ ሴቶች ናቸው፡፡ ፎቶዎቹን ለማየት እዚህ ይጫኑ

በሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ አስተባባሪና የዕለቱ የክብር እንግዳ አቶ ተስፋዬ ቤልጂጌ ባስተላለፉት መልዕክት ትምህርት የማያልቅና ሁሌም እንደ አዲስ የሚቀጥል ቢሆንም አንድ ደረጃ ላይ ተምሮ መመረቅና ለቀጣይ ሕይወት መዘጋጀት በጣም አስደሳች ነው ብለዋል፡፡

የሀገር ዕድገት የሚለካው በተገነቡ ትላልቅ ሕንጻዎችና ረዣዥም መንገዶች ብቻ አይደለም ያሉት አቶ ተስፋዬ ይልቁንም የተማሩ፣ አምራችና ከስሜታዊነት ይልቅ በምክንያታዊነት የሚያምኑ ሀገር ተረካቢ ትውልድ መፍጠር ሲቻል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ስለሆነም ተመራቂዎች በየተማራችሁበት የትምህርት ዘርፍ ሀገራችን የተያያዘችውን የዕድገት፣ የሠላም፣ የዲሞክራሲና የብልጽግና ጉዞ በተሳካ መልኩ ለማስቀጠል የበኩላችሁን ትልቅ ኃላፊነት እንድትወጡ ሲሉ በአጽንዖት አሳስበዋል፡፡

የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛ በበኩላቸው ተመራቂዎች ከዩኒቨርሲቲው በገበያችሁት ዕውቀትና ክሂሎት እንዲሁም መልካም ሥነ-ምግባርን በመላበስ የሥራ ዓለምን ተቀላቅላችሁ የሀገራችንን ሰላምና ልማት ለማረጋገጥ መንግሥትና ሕዝብ እያደረጉ ባሉት ጥረት ውስጥ የበኩላችሁን አስተዋጽዖ ለማበርከት ልትዘጋጁ ይገባል ብለዋል፡፡

ከተመራቂዎቹ መካከል ተማሪ ደረጀ ደስታ ከኮኦፕሬቲቭ አካውንቲንግና ኦዲቲንግ ትምህርት ክፍል 3.95 በማምጣትና 27A+ በማስመዝገብ የካምፓሱ የዋንጫ ተሸላሚ ሲሆን ተመራቂ ተማሪ ሙሉዓለም ዋለልኝ ከቢዝነስ አስተዳደርና ኢንፎርሜሽን ሲስተም ትምህርት ክፍል 3.89 በማምጣትና 14A+ በማስመዝገብ ከሴቶች ከፍተኛውን ውጤት በማግኘቷ የወርቅ ሀብል ተሸላሚ ሆናለች።

የዋንጫ ተሸላሚ ተመራቂ ተማሪ ደረጀ ደስታ ስኬታማ ለመሆን እችላለሁ ብሎ መነሳት፣ ተስፋ አለመቁረጥና ስህተቶችን በማረም ሳይታክቱ መሥራት እንደሚገባ ተናግሯል፡፡ ከሰላም አኳያም ወጣቶች አዕምሯቸውን ሰፋ አድርገው ማሰብና ለሀገርና ለዓለም የመፍትሄ ሰው መሆንን መምረጥ አለባቸው ብሏል፡፡

ከሴቶች ከፍተኛውን ውጤት ያመጣችው ተመራቂ ሙሉዓለም ዋለልኝ በበኩሏ ወደ ስኬት ለመድረስ ጥረት እንደሚያስፈልግ ተናግራ የመንግሥት ሥራ ሳልጠብቅ በግሉ ዘርፍ ስኬታማ ሥራ ፈጣሪ ለመሆን ዓላማ አለኝ ብላለች፡፡ ወጣቶች ከብሔርተኝነትና ሃይማኖትን መሠረት ካደረጉ ግጭቶች ርቀው የሀገርን ሰላምና ብልጽግና ለማስጠበቅ እንዲተጉም መልዕክቷን አስተላልፋለች፡፡

የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት