ዩኒቨርሲቲው ከእድገቱ ጋር በሚመጣጠን ሁኔታ አቅሙን ለማሳደግ ከሚያደርገው ዘርፈ ብዙ ማሻሻያዎች መካከል የትምህርት ፕሮግራሞችን ጥራትና አግባብነት በመገምገም የሚያከናውነው የማስፋፊያ ሥራ አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ በዚህም ለአገሪቱ ሁለንተናዊ ለውጥ አጋዥ ሊሆን በሚችል አግባብ  በቴክኖሎጂ፣ በኢንደስትሪ፣ በጤና፣ በማህበራዊ፣ በግብርና እና በሌሎችም በርካታ መስኮች የትምህርት ፕሮግራሞችን በመክፈት ጥራት ያለው ትምህርት በመስጠት ብቃት ያላቸው ባለሙያዎችን በጥራትና በብዛት በማፍራት በአገራችን ካሉ አንጋፋና ስመ-ጥር ተቋማት መካከል ግንባር ቀደም ነው፡፡ ምስሎቹን ለማየት እዚህ ይጫኑ::

የትምህርት ፕሮግራሞችን ጥራት፣ አግባብነትና ተወዳዳሪነት የተሻሉ ለማድረግ በሥርዓተ ትምህርት ቀረጻ ወቅት የባለሙያዎች አስተያየት፣ ድጋፍና ክትትል እንዲሁም የውስጥና የውጪ ስርዓተ ት/ት ግምገማ በወጥነት ሁሌም የምንፈጽማቸው ተግባራት መሆናቸው ይታወቃል፡፡

በተጨማሪም ማናቸውም ፕሮግራሞች ተግባራዊ ከመሆናቸው በፊት በዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ አሠራር፣ ደንብና ሥርዓት በዩኒቨርሲቲው ሴኔት ተገምግሞ፣ ፀድቆና በአስተዳደር ቦርድ ተቀባይነት ሲያገኝ  እንዲሁም በት/ት ሚኒስቴር ከፍተኛ ትምህርት ዘርፍ ዕውቅና ተሰጥቶት ተግባራዊ እንደሚሆን ይታወቃል፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞ በትምህርት ሚኒስቴር ከከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ በ17/12/2006 በቁጥር 7/ጠ-259/3675/06 አዳዲስ የፕሮግራም አከፋፈትን በሚመለከት የተፃፈን መመሪያ መሠረት በማድረግ ለ2007  የትምህርት ዘመን በመጀመሪያ ዲግሪ አዳዲስ ፕሮግራሞችን ለመጀመር ሥርዓተ ትምህርት(ካሪኩለም) ተቀርጾ በሴኔት ከፀደቁና በቦርድ ተቀባይነት ካገኙ ሰባት የትምህርት ፕሮግራሞች መካከል በወቅቱ በቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሥር በሚገኘው በሜካኒካል ትምህርት ክፍል በአሁኑ የሜካኒካልና ፕሮዳክሽን ምህንድስና ፋካልቲ ሥር የሚገኘው ሜታል ፕሮዳክሽን ኢንጂነሪንግ (Metal Production Engineering) ትምህርት ፕሮግራም አንዱ ነው፡፡

ነገር ግን ይህን እውነታ ወደ ጎን በመተው ተገቢ ባልሆነና ህግና ደንብን በጣሰ አኳኋን የዩኒቨርሲቲውን ፕሬዝደንት፣ የአካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዝደንትንም ጨምሮ ሌሎችም አመራሮች ፕሮግራሙ በዩኒቨርሲቲው እየተሰጠ መሆኑን እንደማያውቁ ተደርጎ በማህበራዊ ሚዲያ (በFacebook) ሐላፊነት በጎደለው መንገድ የተሳሳተ መረጃ (Seyoum Teshome) ስዩም ተሾመ  እና GMN (Gamo Media Network) በተባሉ የፌስቡክ ገፆች ላይ ወጥቷል፡፡

ጉዳዩን በተመለከተ የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዝደንት ዶ/ር የቻለ ከበደ ትምህርት ክፍሉ በወቅቱ በሜቴክ በቀረበው ጥያቄ መሠረት ሥርዓተ-ትምህርት ተዘጋጅቶለት ሥርዓተ-ትምህርቱ የውስጥና የውጪ ሥርዓተ-ትምህርት ግምገማ ተደርጎለት በሴኔትና በቦርድ ፀድቆ “Metal Production Engineering” በሚል ስያሜ እንደተከፈተ ገልፀዋል፡፡ እንደ ም/ፕሬዝደንቱ ትምህርት ክፍሉ በዩኒቨርሲቲው እንዳለ የዩኒቨርሲቲው አመራሮች አያውቁም ተብሎ የተሰራጨው መረጃ መሠረተቢስና ሀሰት መሆኑን እንዲሁም ፕሮግራሙን ፅ/ቤታቸውም ሆነ ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ በቅርበት በተለያዩ ጉዳዮች የሚደግፉት መሆኑን አሳውቀዋል፡፡  ሥርዓተ-ትምህርቱ ክለሳ ተደርጎለት Metal Production Engineering የነበረው ስያሜ ወደ Production Engineering  እንዲቀየር በቅርቡ የተወሰነ ቢሆንም የተደረገውን የስያሜ ለውጥ  የማስተዋወቅ በቂ ሥራ ባለመሰራቱ ምክንያት በተወሰነ ደረጃ የግንዛቤ ችግር ሊፈጠር ችሏል ብለዋል ፡፡

ዩኒቨርሲቲዎች ከቀጣሪ ድርጅቶች በሚቀርቡ ጥያቄዎችና የሰው ኃይል ፍላጎት ጥናትን መሰረት በማድረግ የትምህርት ፕሮግራሞችን መክፈት የተለመደ አሰራር መሆኑን የተናገሩት ዶ/ር የቻለ ይህም ፕሮግራም ከሜቴክ በቀረበው ጥያቄ  እንዲሁም በወቅቱ በተደረገ የገበያ ፍላጎት ዳሳሳ ጥናት መሠረት የተከፈተ መሆኑንና ይህም ህጋዊ አሰራር መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ዶ/ር የቻለ በተጨማሪም በዩኒቨርሲቲው የተማሪዎች ሰላማዊ ሰልፍ ያልተደረገ መሆኑንና በአንፃሩ ግን ከተማሪዎች ጋር በጉዳዩ ዙሪያ ውይይት ተካሂዶ ዩኒቨርሲቲው የትምህርት መስኩን ባጭር ጊዜ ውስጥ የማስተዋወቅ ሥራ ለመስራት በመስማማት ከተማሪዎች ጋር መግባባት መቻሉን ገልፀዋል፡፡ ትምህርት ክፍሉን በመክፈት ግለሰቦችም ሆኑ ተቋማት የሚያገኙት ምንም አይነት ያልተገባ ጥቅም እንደሌለም በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡

የሜካኒካልና ፕሮዳክሽን ምህንድስና ፋካልቲ ሥር የሚገኘው የሜታል ፕሮዳክሽን ምህንድስና ትምህርት ክፍል (Metal Production Engineering department) ተማሪዎች በቀን 24/03/2011 ዓ/ም ባነሱት የግልፀኝነት ጥያቄ ዙሪያ ከቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩትና ከፋካልቲ ኃላፊዎች ጋር ውይይት አድርገዋል፡፡

በመጨረሻም (Seyoum Teshome) ስዩም ተሾመ  እና GMN (Gamo Media Network)በተባሉ የፌስቡክ ገፆች በቀረበው ከእውነት የራቀና  የተሳሳተ መረጃ ሆን ተብሎ የተቋሙን ዝና የማጉደፍ፣ በተቋሙ እየተካሄዱ ያሉ ለውጦችን የማደናቀፍ እንዲሁም የሚዲያ ሕግና ደንብን ኃላፊነት በጎደለው ሁኔታ በመጣስ የግልንና የቡድንን ርካሽ ፍላጎት ለማሳካት የተቋሙንና የዘርፉን ኃላፊዎች  ያለአግባብ የማሳጣትና የመወንጀል ተግባር ተፈፅሟል፡፡

ስለሆነም ዩኒቨርሲቲው የቀረበው መረጃ የተሳሳተ መሆኑን እያረጋገጠ ለህብረተሰቡ መሰልና መሰረተ ቢስ መረጃዎችን የሚያቀርቡ አካላትን ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ እያሳሳበ ለተፈጠረውና ከዚህም በኋላ ሊፈጠሩ የሚችሉ ጉዳዮችን በህግ አግባብ እርምጃዎች እንዲወሰዱ የሚያደርግ መሆኑን ያስታውቃል፡፡

ኮርፖሬት ኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት