Print

አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ከ‹‹AMU-IUC›› ፕሮጀክት V ጋር በመተባበር ‹‹Evidence-based Training for Model Farmers and Stakeholders on Solutions to Challenges of Enset Production and Livestock Feed Security in Gamo Zone, Southern Ethiopia›› በሚል ርእስ ከጋሞ ዞን ሰባት ወረዳዎች ለመጡ አርሶ አደሮችና የዘርፉ ባለሙያዎች ከሐምሌ 05-08/2015 ዓ/ም ሥልጠና ሰጥቷል፡፡ ተጨማሪ ፎቶዎችን ለማየት እዚህ ይጫኑ፡፡

በሥልጠናው ‹‹Manure Management and Nutrient Loss During Storage››፣ ‹‹Enset Macro Propagation and Media Preparation››፣ ‹‹Enset Bacterial Wilt and its Management››፣ ‹‹Mistakes during Bacterial Wilt Management, Practical Training on Enset Bacterial Wilt Symptoms››፣ ‹‹Optimizing of Livestock Feed Security Via Biomass Fermentation, Preparation of Multi-Nutrient Blocks (MNB),Practical Training Feed Conservation Via Fermentation›› በሚሉ ርእሶች ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡

የግብርና ሳይንስ ኮሌጅ ዲን ዶ/ር ደግፌ አሰፋ እንሰት ከሰው ምግብነት ባለፈ ለእንስሳት መኖነት የሚውልና ድርቅን የመቋቋም አቅም ያለው በመሆኑ ምርቱን በማሻሻል የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና እሴት ተጨምሮበት ለእንስሳት መኖነት እንዲውል በዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ ሥራ እየተሠራ ነው፡፡ በዚህ ረገድ የAMU-IUC ፕሮግራም ፕሮጀክት V በተለይም በእንሰትና እንስሳት ጤናና እርባታ ዘርፍ መምህራንን በ2ና 3ዲግሪ በማሠልጠን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረገ ነው ብለዋል፡፡

የAMU-IUC ፕሮጀክት ማኔጀር ዶ/ር ፋሲል እሸቱ እንደገለጹት ፕሮጀክት V በፕሮግራሙ ከተካተቱት ሰባት ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ ሲሆን ቀጣይነት ያለው የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ይሠራል። የእርሻ ሥራ ሰብሎችና ፍራፍሬዎች ማምረት ብቻ ሳይሆን እንስሳት እርባታንም ያቀፈ በመሆኑ የግብርና ሥራዎችን ከተፈጥሮ ጋር በማይቃረን መልኩ ሂደቱን በማዘመን ምርትና ምርታማነትን ማሻሻል እንዲሁም የኅብረተሰቡን ኢኮኖሚ ማዳበር የሚያስችሉ የምርምር ውጤቶችን ማምጣት የፕሮጀክቱ ዓላማ መሆኑን ዶ/ር ፋሲል ተናግረዋል፡፡ እንደ ዶ/ር ፋሲል መሰል በጥናት ላይ የተመሠረቱ ሥልጠናዎች ሳይንሳዊ ግኝቶችን ለኅብረተሰቡ በማሳየት፣ በማሰራጨት እና በማረጋገጥ ረገድ ትልቅ ሚና ይጫወታሉ።

የAMU-IUC ፕሮጀክት V አስተባባሪ ፕ/ር ይስሃቅ ከቸሮ ፕሮጀክቱ በተለይ በሰብል፣ በሆርቲካልቸር፣ በአፈር፣ በሰብል ተረፈ-ምርቶችና በእንስሳት እርባታ ላይ የሚሠራ መሆኑን ተናግረው በምርምር የተገኙ ውጤቶችንና ምርጥ ተሞክሮዎችን ለአርሶ አደሩ ማውረድ እንዲቻል ሥልጠናው ተዘጋጅቷል ብለዋል፡፡ እንደ ፕ/ር ይስሃቅ ሥልጠናውን ከሚሰጡት መካከል በዩኒቨርሲቲው AMU-IUC ፕሮግራም አማካኝነት ከእንሰትና የእንስሳት ምርትን ከማሻሻል ጋር በተገናኘ ከዚህ ቀደም ወደ ቤልጂዬም ሀገር ሄደው 3ዲግሪያቸውን አጠናቀው የመጡ መምህራን የሚገኙ ሲሆን ባገኙት ዕውቀት በመታገዝ መረጃዎችን ከአርሶ አደሮች ማሳ በመሰብሰብ በጥናታቸው የተገኙ ውጤቶችን ለአርሶ አደሮች ለማውረድና የዕውቀት ሽግግር እንዲፈጠር ሥልጠናው ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው፡፡

በሥልጠናው ማጠናቀቂያ ተሳታፊዎች የአካባቢውን የሙቀትና የዝናብ መጠን በመቆጣጠር ችግኞች በአጭር ጊዜ ውስጥና በስፋት መድረስ እንዲችሉ የሚያግዝ የአፈርና የእንስሳት ዕዳሪ ቅልቅል ማባዣና መሞከሪያ ጣቢያን (Tunnel) ተዘዋውረው ተመልክተዋል፡፡ ለምርምርና ለመማር ማስተማር ሥራ እንዲያግዝ የተገዛ በኤሌክትሪክ የሚሠራ እና በኮሌጁ መምህራን የተሠራ በእጅ የሚዘወር የእንስሳት መኖ ማቀነባበሪያና መፍጫ ማሽኖች፣  ከተፈጨው የመኖ ድርቆሽ ጋር የስኳር ፋብሪካ ተረፈ ምርትን (ሞላሰስ) አየር በማይገባበት ዕቃ ለ2 ሳምንታት በማስቀመጥ ውጤታማ የእንስሳት መኖ አዘገጃጀት እንዲሁም በቤት ውስጥ የዓሣ ገንዳን በማዘጋጀት ዓሣን ማርባት የሚያስችል ቤተ ሙከራ በማሳያነት ተጎብኝተዋል፡፡

አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ

የብሩህ ተስፋ ማዕከል!

ለተጨማሪ መረጃ በድረ-ገጽና በማኅበራዊ ትስስር ገጾቻችን ይከተሉን፡-

ድረ-ገጽ - https://www.amu.edu.et/

ቴሌግራም - https://t.me/arbaminch_university

ፌስቡክ - https://www.facebook.com/ArbaMinchUniversityCCD/

ዩቲዩብ - https://www.youtube.com/channel/UCOO_nclhMo8M3r74OyPBlVA

የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት