Print

ዶ/ር ብሩክ አማረ ስራቴ ከአባታቸው ከአቶ አማረ ስራቴ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ አልማዝ አበበ በጋሞ አውራጃ አርባ ምንጭ ከተማ መስከረም 6/1977 ዓ/ም ተወለዱ፡፡ 

ዶ/ር ብሩክ ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን በአርባ ምንጭ ጫሞ 1 ደረጃ ትምህርት ቤት እና የ2 ደረጃ ትምህርታቸውን በአርባ ምንጭ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አጠናቀዋል፡፡

ዶ/ር ብሩክ አማረ ከሀዋሳ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ በሰውነት ማጎልመሻ ትምህርት ዘርፍ በዲፕሎማ፣ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከኮተቤ ሜትሮፖሊታን ዩኒቨርሲቲ/Metropolitan University/ በጤናና ሰውነት ማጎልመሻ መስከረም 13/2002 ዓ/ም፣ የሁለተኛ ዲግሪያቸውን ከሐሮማያ ዩኒቨርሲቲ በኮቺንግና ቴራፒ/Coaching & Therapy/ ሰኔ 29/2005 ዓ/ም እንዲሁም የሦስተኛ ዲግሪያቸውን በስፖርት እና ኤክሰርሳይስ ሕክምና/Sports and Exercise Medicine/ ሕንድ ሀገር ከሚገኘው ፐንጃቢ ዩኒቨርሲቲ/Punjabi University/ ተከታትለው ተመርቀዋል፡፡

ዶ/ር ብሩክ በጅማ ዩኒቨርሲቲ ከመስከረም 21/2001 - መስከረም 13/2002 ዓ/ም በቴክኒካል ረዳት I፣ ከመስከረም 14/2002 ዓ/ም - መስከረም 12/2003 ዓ/ም  በረዳት ምሩቅ 1፣ ከመስከረም 2003 ዓ/ም - መስከረም 10/2004 ዓ/ም በረዳት ምሩቅ 11፣ ከመስከረም 2004 ዓ/ም - ሰኔ 28/2005 ዓ/ም በረዳት ሌክቸረርነት እና ከሰኔ 29/2005 ዓ/ም - ኅዳር 28/2009 ዓ/ም በሌክቸረርነት አገልግለዋል፡፡

ዶ/ር ብሩክ ከኅዳር 1/2013 ዓ/ም - የካቲት 19/2015 ዓ/ም በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በተፈጥሮና ቀመር ሳይንስ ኮሌጅ በስፖርት ሳይንስ ትምህርት ክፍል በረዳት ፕሮፌሰርነት አካዳሚክ ማዕረግ በመምህርነት እንዲሁም ከየካቲት 20/2015 ዓ/ም ጀምሮ ሕይወታቸው እስካለፈበት ጊዜ ድረስ ትምህርት ክፍሉን በኃላፊነት ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡   

ዶ/ር ብሩክ ባለትዳርና የሁለት ወንድና የአንዲት ሴት ልጆች አባት ሲሆኑ ባጋጠማቸው ድንገተኛ ሕመም በሕክምና ሲረዱ ቆይተው መስከረም 10/2016 ዓ/ም በ39 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡

አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በዶ/ር ብሩክ አማረ ኅልፈት የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን እየገለጸ ለቤተሰቦቻቸው፣ ለሥራ ባልደረቦቻቸውና ለወዳጅ ዘመዶቻቸው እንዲሁም ለዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ መጽናናትን ይመኛል፡፡

አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ

የብሩህ ተስፋ ማዕከል!

ለተጨማሪ መረጃ በድረ-ገጽና በማኅበራዊ ትስስር ገጾቻችን ይከተሉን፡-

ድረ-ገጽ - https://www.amu.edu.et/

ቴሌግራም - https://t.me/arbaminch_university

ፌስቡክ - https://www.facebook.com/ArbaMinchUniversityCCD/

ዩቲዩብ - https://www.youtube.com/channel/UCOO_nclhMo8M3r74OyPBlVA

የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት