በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪ የተዘጋጀውና የእንሰት እርሾን ለረዥም ጊዜ በቤተ-ሙከራ ለማስቀመጥና ለአርሶ አደሮች አባዝቶ ለማከፋፈል ያለመው ፕሮጀክት ከዓለም ዓቀፉ የዘረመል ምኅንድስና እና ባዮቴክኖሎጂ ማዕከል የ45 ሺህ ዩሮ ድጋፍ አግኝቷል፡፡

የፕሮጀክቱ ዋና ተመራማሪ ዶ/ር አዲሱ ፈቃዱ እንደገለጹት ዓለም ዓቀፉ የዘረመል ምኅንድስና እና ባዮቴክኖሎጂ ማዕከል በትምህርት፣ በሥልጠናና ቤተ-ሙከራዎችን በማደራጀት የአዳዲስ ሳይንቲስቶችን አቅም ለማሳደግ በመላው ዓለም ለሚገኙ የመስኩ ተመራማሪዎች በየዓመቱ የምርምር ፕሮጀክት ጥሪ ያስተላልፋል፡፡ እ.ኤ.አ በ2020 ባስተላለፈው ጥሪ መሠረት ከ50 አባል ሀገራት ከቀረቡ 170 የምርምር ፕሮጀክት ንድፈ ሃሣቦች መካከል ፕሮጀክታቸው ከኢትዮጵያ ሊመረጥ መቻሉን ዶ/ር አዲሱ ተናግረዋል፡፡

እንደ ዶ/ር አዲሱ ገለጻ ፕሮጀክቱ ከታኅሣሥ 23/2013 ዓ/ም ጀምሮ ወደ ሥራ የሚገባ ሲሆን የእንሰት እርሾን በቤተ-ሙከራ ለረዥም ጊዜ ማስቀመጥ የሚቻልበት ዘዴና እርሾውን አባዝቶ ለአርሶ አደሩ ማዳረስን ዓላማ አድርጓል፡፡ ይህንን ለማሳካት እንዲሁም ለቀጣይ ምርምሮች እንዲረዳ ጭምር ለሙከራዎቹ የሚያስፈልጉ ቋሚና አላቂ ዕቃዎችን በማሟላት የዩኒቨርሲቲውን ባዮቴክኖሎጂ ቤተ-ሙከራ የማደራጀት ሥራ በፕሮጀክቱ ይሠራል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ተመራማሪዎችና የቤተ-ሙከራ ባለሙያዎች በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ የሚዘጋጁ አጫጭር የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠናዎችና ወርክሾፖችን እንዲሳተፉም ይመቻቻል፡፡ አጫጭር ሥልጠናዎቹ በርካታ ባለሙያዎችን የሚያሳትፉና በቤተ-ሙከራዎች የሚታዩ የክሂሎት ክፍተቶችን የሚሞሉ ናቸው፡፡

የእንሰት እርሾን ሳይበላሽ እስከ 20 ዓመት ድረስ በቤተ-ሙከራ ማስቀመጥ እንደሚቻል የሚናገሩት ዶ/ር አዲሱ በፕሮጀክቱ በሚካሄደው ምርምር እርሾውን ለረዥም ጊዜ ከማስቀመጥ ባሻገር በቤተ-ሙከራ በማባዛት ወደ አርሶ አደሩ በማድረስ በቆጮ ጥራት ላይ ያመጣው ለውጥ ግብረ መልስ የሚሰበሰብ ይሆናል፡፡

መቀመጫውን ጣሊያን ሀገር ያደረገው ዓለም ዓቀፉ የዘረመል ምኅንድስና እና ባዮቴክኖሎጂ ማዕከል በዘርፉ የምርምር፣ የሥልጠናና የቴክኖሎጂ ሽግግር የልኅቀት ማዕከል ሆኖ ለማገልገል ያለመና ከ60 በላይ ቋሚ አባል ሀገራትን ያቀፈ ተቋም ሲሆን ኢትዮጵያም ከአባል ሀገራቱ መካከል አንዷናት፡፡ በኢትዮጵያ በባዮቴክኖሎጂና ዘረመል ምኅንድስና ዘፍር የሚከናወኑ ምርምሮችን የኢትዮጵያ ባዮቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት በበላይነት ያስተባብራል፡፡

የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት