አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ብዝሃ ሕይወት ምርምርና ጥበቃ ማዕከል ‹‹Restoring Degraded Forest Ecosystem in the Rift Valley Escarpments of the Gamo Zone ,South Ethiopia for Improved Services and Biodiversity Conservation›› በተሰኘ ርዕሰ ጉዳይ ዙሪያ የሚሰራ ለ5 ዓመታት የሚቆይ አዲስ የምርምር ፕሮጀክት ባለድርሻ አካላት በተገኙበት መጋቢት 15/2017 ዓ/ም በይፋ አስጀምራል፡፡ ተጨማሪ ፎቶዎችን ለማየት እዚህ ይጫኑ፡፡

የዩኒቨርሲቲው የምርምርና ትብብር ም/ፕሬዝደንት ዶ/ር ተክሉ ወጋየሁ የደን መራቆትና መመናመን ዓለም ዓቀፋዊና ሃገራዊ ችግር በመሆኑ የአከባቢ ጥበቃ ሥራዎችን ማከናወን የሕልውና ጉዳይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ደን የምንጠጣው ውኃም ጭምር ስለሆነ ውኃ እንዲኖር ተራራና ደንን መጠበቅና የተመናመነን ደን ለመመለስ መሥራት ግዴታ መሆኑንም ዶ/ር ተክሉ አውስተዋል፡፡

የምርምር ጉዳዮች ኤክሰኪዩቲቭ ዳይሬክተር ዶ/ር ተስፋዬ ሀብተማርያም ዩኒቨርሲቲው በብዙ መልኩ ማኅበረሰብ ተኮር ሥራዎችን እየሰራ እንዳለ ጠቁመው የተራቆቱ ቦታዎችን መልሶ በማልማት ሥራ ላይ ዘርፈ ቡዙ ተግባራትን እያከናወነ መቆየቱን ተናግረዋል፡፡ ሊሰራ የታቀደው ፕሮጀክት ማኅበረሰብ ተኮር መሆኑን የገለጹት ዶ/ር ተስፋዬ ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ 1.75 ሚሊየን ብር መመደቡን ተናግረዋል፡፡ ሥራው በእጅጉ ጠቃሚና ሰፊ መሆኑን ያወሱት ዳይሬክተሩ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያለሆኑ ድርጅቶች ለፕሮጀክቱ ስኬትና ውጤታማነት እንዲተባበሩም ጠይቀዋል፡፡

የብዝሃ ሕይወት ምርምርና ጥበቃ ማዕከል ዳይሬክተር ዶ/ር ሽቴ ጋተው ፕሮጀክቱ የተጎዱ ቦታዎችን መልሶ ለማልማት የሚሰራ መሆኑንና በተለያዩ ምክንያቶች የተራቆቱ ቦታዎችን ወደ ነበሩበት በመመለስ የአካባቢን ብዝሃ ሕይወት መልሶ እንዲያገግም ማድረግ ላይ ያተኮረ ነው፡፡ በፕሮጀክቱ የተያዘው ሥራ ሰፊ ጊዜና ጉልበት የሚጠይቅ በመሆኑ ባለድርሻ አካላትን በልዩ ትኩረት በማሳተፍ ለመስራት መታቀዱንም አብራርተዋል፡፡ ፕሮጀክቱ ሀገሪቱ ከያዘችው የአረንጓዴ ልማት አቅጣጫ ጋር አብሮ የሚሄድና ለሀገራዊ ውጥኑ ስኬት የበኩሉን የሚያበረክት መሆኑንም ዶ/ር ሽቴ አውስተዋል፡፡

የተፈጥሮና ቀመር ሳይንስ ኮሌጅ ዲን ዶ/ር ቴዎድሮስ ብርሃኑ እንደገለጹት ጋሞ ዞን የበርካታ ደኖች እንዲሁም ብዝሃ ሕይወት መገኛ ቢሆንም በተለያዩ ሰው ሰራሽና ሌሎች ምክንያቶች ብዝሃ ሕይወቱ አደጋ ተጋርጦበታል፡፡ ይህን አደጋ ለመግታትና  እየጠፋ ያለውን ደን ሕልውና ጠብቆ ማቆየትና ወደ ነበረበት መመለስ የዚሀ ትውልድ አደራና ግዴታ ነውም ብለዋል፡፡

የብዝሃ ሕይወት ምርምርና ጥበቃ ማዕከል ተመራማሪና የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ዶ/ር ተመስገን ዲንጋሞ ፕሮጀክቱ ሁለት ዓላማዎች ያሉት መሆኑን ጠቅሰው የአከባቢውን ገጽታ፣ የእጽዋት ስብጥር፣ የአከባቢው የአየር ንብረት ለውጥና ሌሎች ጉዳዮች ዙሪያ ጥናት ማካሄድ አንደኛው ሲሆን የማገገሚያ ስልቶችን በማዘጋጀት መልሶ የማልማት ሥራዎችን መሥራት ሁለተኛው ዓላማ ነው ብለዋል፡፡ ፕሮጀክቱ በአርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ ላንቴ፣ ጫኖ ዶርጋ፣ ቆላ ሼሌ፣ ኤልጎ  አከባቢዎች ላይ የሚተገበር መሆኑንም ዶ/ር ተመስገን አመላክተዋል፡፡

በግብርና ሳይንስ ኮሌጅ የደን ሳይንስ ትምህርት ክፍል መምህራና ተመራማሪ እንዲሁም የፕሮጀክቱ አባል ዶ/ር ዮናስ ኡጎ በፕሮጀክቱ የተራቆቱ ደኖችን ሥነ ምኅዳር መልሶ ለማልማት እንደሚሰራና ሥራው በተመረጡ ውስን ቦታዎች ላይ የሚተገበር መሆኑን አመላክተዋል፡፡ የደን መመናመን ምርትና ምርታማነትን የሚቀንስ ሲሆን የመሬት ናዳ፣ የአፈር መሸርሸር፣ የጎርፍና ሌሎች ጉዳቶችን እንደሚያመጣም አክለዋል፡፡

የውይይቱ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት የፕሮጀክት ሥራው ለማኅበረሰቡ እጀግ ጠቃሚ፣ አስፈላጊና ወቅታዊ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ በመሆኑም ለሥራው ስኬት በቁርጠኝነት ለመስራት እና የሚጠበቅባቸውን ሚና ለመወጣት ዝግጁነታቸውን አረጋግጠዋል፡፡

በዕለቱ የዘርፉ ባለሙያዎች፣ የቀበሌና የወረዳ አሰተዳደሮች፣ የግብርና ጽ/ቤት ኃላፊዎች ተሳትፈዋል፡፡

ለተጨማሪ መረጃ በድረ-ገጽና በማኅበራዊ ትስስር ገጾቻችን ይከተሉን፡-

ድረ-ገጽ - https://www.amu.edu.et/

ቴሌግራም - https://t.me/arbaminch_university

ፌስቡክ - https://www.facebook.com/ArbaMinchUniversityccd/

ዩቲዩብ - https://www.youtube.com/channel/UCOO_nclhMo8M3r74OyPBlVA

የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሥራ አስፈጻሚ ጽ/ቤት