- Details
በኢትዮጵያ የሲቪል ምህንድስና ተማሪዎች ማህበር ድጋፍ በዩኒቨርሲቲው ለመጀመሪያ ጊዜ በወቅታዊ የሲቪል ምህንድስና ሥራ ልምዶች ላይ ያተኮረ ሲምፖዚዬም ግንቦት 4/2006 ዓ/ም ተካሂዷል፡፡ በሲምፖዚዬሙ ከሲቪል ምህንድስና ጋር የተያያዙ ሙያዊ ጉዳዮችን በሚመለከት በሲቪል ምህንድስና ትምህርት ክፍል መምህራንና ተማሪዎች የተለያዩ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡
በዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተርና የእለቱ የክብር እንግዳ ዶ/ር ነጋሽ ዋጌሾ እንደገለጹት በአገራችን በምህንድስናው መስክ በአለም አቀፍ ደረጃ ያሉ ተጽዕኖዎች መጎልበት በመቻላቸው የኮንስትራክሽን ኢንደስትሪው ከማደጉም አልፎ ለምዕተ ዓመቱ የልማት ግቦች ስኬት የበኩሉን በመወጣት ላይ ነው፡፡ ኢንደስትሪው በግልም ሆነ በመንግሰት የሚጠይቀው የሰው ኃይል በእጅጉ በመጨመሩ በዘርፉ በእውቀትና በክህሎት የዳበሩ ባለሙያዎችን ማፍራት ወሳኝ ነው ያሉት ዳይሬክተሩ ይህን መሰል ፎረሞች መዘጋጀታቸው ሙያዊ አቅምን ለማሳደግና እርስ በእርስ ለመማማር እንደሚያግዝ ተናግረዋል፡፡
የአገሪቱ የልማት ህዳሴ በቴክኖሎጂ እንዲታገዝ በማድረጉ ረገድ በሲቪል ምህንድስና የሙያ መስክ የሚሰለጥኑ ተማሪዎች ሚና የጎላ በመሆኑ ማህበሩ ይህን ለመደገፍና አቅማቸው እንዲጎለብት ለማድረግ እንቅስቃሴዎችን እያደረገ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡
በሲምፖዚዬሙ የዩኒቨርሲቲው አመራሮች፣ በቴክኖሎጂ ኢንሲትቲዩት የሚገኙ የትምህርት ክፍል ኃላፊዎች፣ መምህራን እንዲሁም የሲቪል ምህንድስና የዘንድሮ ተመራቂ ተማሪዎችን ጨምሮ ከ150 በላይ ተሳታፊዎች ተገኝተዋል፡፡
የኢትዮጵያ የሲቪል ምህንድስና ተማሪዎች ማህበር በ2004 ዓ/ም ህጋዊ እውቅና አግኝቶ የተቋቋመ ሲሆን የዘርፉ ተማሪዎች ከሙያው የሚጠበቀውን ክህሎት እንዲያገኙ በማድረግ በታማኝነትና በጥሩ ስነ-ምግባር የታነፁ እንዲሁም የበቁ ምሁራንን በማፍራት ያደገች ኢትዮጵያን ለመፍጠር የሚያስችል ራዕይን አንግቦ የሚንቀሳቀስ ማህበር ነው፡፡
- Details
የሥርዓተ ፆታ ዳይሬክቶሬት ለ20 የዩኒቨርሲቲው ሴት መምህራንና ረዳት የቴክኒክ ባለሙያዎች ከግንቦት 7 እስከ 9/2007 ዓ/ም በህይወት ክህሎትና አመራር ሰጪነት ሚና ዙሪያ የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ሰጥቷል፡፡
በሥነ-ልቦና እና በማኔጅመንት ትምህርት ክፍል መምህራን የተሰጠው ሥልጠና ዓላማ የመምህራኑን በራስ መተማመን በማጎልበት የችግር ፈችነትና ውሳኔ ሰጪነት ሚናቸው ከፍ እንዲል ማገዝ መሆኑን በዩኒቨርሲቲው የስርዓተ-ፆታ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ወ/ሪት ሙኒት መኩሪያ ተናግረዋል፡፡
በሀገራችን በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሴት መምህራን ቁጥርና በኃላፊነት ደረጃ ያላቸው ተሳትፎ እያደገ ቢሆንም የሚፈለገው ደረጃ ላይ አለመድረሱን ያወሱት ዳይሬክተሯ ለዚህም ሴቶች ከተለያዩ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ ተፅዕኖዎች ሙሉ በሙሉ አለመላቀቃቸው እንደ ምክንያት ይጠቀሳሉ ብለዋል፡፡
የሴቶችን ተሳትፎ በማሳደግ የሚጠበቅባቸውን ሀገራዊ አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ለማስቻል እነዚህን ተጽዕኖዎችንና እንቅፋቶችን በመቅረፍ በራስ መተማመናቸውን እንዲጨምሩና የውሳኔ ሰጪነት ሚናቸውን እንዲያጎለብቱ ማድረግ እንደሚያስፈልግም ዳይሬክተሯ ገልፀዋል፡፡
ዳይሬክቶሬቱ የዩኒቨርሲቲውን የአስተዳደር ዘርፍ ሴት ሠራተኞች እንዲሁም ሴት መምህራንና ተማሪዎችን ለመደገፍ እቅድ አዘጋጅቶ እየተንቀሳቀሰ ሲሆን ለውጥ ያመጣሉ ተብለው በሚታሰቡ ጉዳዮች ባለሙያዎችን በመጋበዝ የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠናዎችንና ሌሎች ድጋፎችን እያደረገ ይገኛል፡፡
- Details
የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የመሰረት ድንጋይ የተጣለበትን አራተኛ አመትና የግንባታውን መጋመስ በማስመልከት መጋቢት 29/2007 ዓ/ም ዩኒቨርሲቲው ዕለቱን በተለያዩ ዝግጅቶች አክብሯል፡፡
የግድቡ ግንባታ ኃይል ከማመንጨት ዓብይ ዓላማው ባሻገር ተምሳሌታዊ የሆነ ጠቀሜታ ያለውና የአይቻልም መንፈስን ሰብሮ ወደ ይቻላል መንፈስ ያሸጋገረ መሆኑን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር ፈለቀ ወልደየስ ገልፀዋል፡፡ እየተካሄደ ላለው የልማትና የዲሞክራሲ ሂደት በተለይም ለኢንዱስትሪው ሴክተር በቂ ኃይል በማቅረብ ልማታችንን የሚያፋጥን መሆኑንም ፕሬዝዳንቱ አክለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ህዝብ ከድህነት ለመውጣት እያሳየ ያለውን ጥረት ለማስቀጠል የህዳሴ ግድቡን ጨምሮ የተጀመሩ ልማቶችን ከግብ ለማድረስ ሁሉም ዜጋ በቁርጠኝነት መረባረብ አለበት ሲሉ የዩኒቨርሲቲው ኮርፖሬት ኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ፍስሃ በቀለ አስገንዝበዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው ከምስረታው ጊዜ ጀምሮ የአገራችንን የውሃ ኃብት ለማበልፀግ ታስቦ የተቋቋመ እንደመሆኑ በዘርፉ የሠለጠኑ ምሁራንን ለአገር በማበርከት ግንባር ቀደም ሚና መጫወት እንደሚጠበቅበት እሙን ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የተቋሙ ሠራተኞች የሁለት ወር ደመወዛቸውን መቶ ፐርሰንት በመክፈል ቦንድ የገዙ ሲሆን ተማሪዎችም ከወር ቀለባቸው በመቀነስ ለግንባታው ስኬት ድጋፍ አድርገዋል፡፡
‹‹አሻራችን ያረፈበት ነውና ኩራት ሊሰማን ይገባል!›› ያሉት የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ አባላት ነገ የተሻለች ሀገር እንድትኖረን ለማድረግ ሁሉም ዜጋ ለግድቡ ግንባታ ካለው ላይ በመቀነስ የሚደያደርገውን ድጋፍ ሳያቋርጥ መቀጠል አለበት በማለት አሳስበዋል፡፡
ፕሮግራሙ በተለያዩ የስነ-ጹሁፍ ስራዎች፣መዝሙሮች፣ስፖርታዊ ውድድሮችና በሌሎች አዝናኝ ትዕይንቶች ደምቆ የተከበረ ሲሆን የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች፣የአስተዳደር ድጋፍ ሰጪ ሰራተኞች፣ ተማሪዎችና መምህራን ተሳትፈዋል፡፡
- Details
በዩኒቨርሲቲው የሁሉ አቀፍ ሴክተር ዳይሬክቶሬት ለዩኒቨርሲቲው የበላይ አመራርና ከተለያዩ የስራ ክፍሎች ለተወጣጡ ኃላፊዎች ሰኔ 6/2007 ዓ/ም የኤች.አይ.ቪ/ኤድስ ሜይንስትሪሚንግ ሥልጠና ሰጥቷል፡፡
የሥልጠናው ዋና ዓላማ በኤች.አይ.ቪ/ኤድስ ሜይንስትሪሚንግ ላይ ግንዛቤ በማዳበርና የባለድርሻ አካላትን ተሳትፎ በማሳደግ የጋራ መግባባት ማምጣት መሆኑን በዩኒቨርሲቲው የሁሉ አቀፍ ሴክተር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ታደሰ ዓለሙ ገልጸዋል፡፡
በስልጠናው ‹‹የኤች.አይ.ቪ/ኤድስ ስርጭት በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት›› በሚል ርዕስ በህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ዲን አቶ በኃይሉ መርደኪዮስ እንዲሁም በሜይንስትሪሚንግ ምንነትና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ በአቶ አለሙ ጣሚሶ የተዘጋጁ የውይይት ሰነዶች ቀርበው ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
በቀረቡት የውይይት ሰነዶች መነሻነት ከተሳታፊዎች አስተያየቶችና ጥያቄዎች የተሰነዘሩ ሲሆኑ በባለሙያዎች ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ መሰል ስልጠናዎችን በየደረጃው ባሉ እርከኖች በመስጠት ግንዛቤውን ማዳበር ይገባል ያሉት ተሳታፊዎቹ በዩኒቨርሲቲው በሚገኙ የሥራ ክፍሎች የኤች.አይ.ቪ/ኤድስ ጉዳይ የዕቅድ አካል ሆኖ የክትትልና ድጋፍ ሥርዓት መዘርጋት እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ለኤች.አይ.ቪ/ኤድስ አጋላጭ የሆኑ የኢኮኖሚ ችግሮችን ከመቅረፍ አንጻር ሴት ተማሪዎችንና ሌሎችንም የመደገፍና የመንከባከብ ሥራ ሊታሰብበት ይገባል ብለዋል፡፡
በሁሉ አቀፍ ሴክተር ዳይሬክቶሬት የኤች.አይ.ቪ ኤድስ መከላከልና መቆጣጠር ቡድን አማካኝነት በተሰጠው በዚህ ሥልጠና የዩኒቨርሲቲውን ፕሬዝደንት ጨምሮ ከ40 የሚበልጡ የበላይ አመራሮች፣ ዳይሬክተሮች፣ የሥራና የትምህርት ክፍል ኃላፊዎች ተሳትፈዋል፡፡
- Details
በማህበራዊ ሳይንስና ስነ-ሰብ እንዲሁም በቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጆች አዘጋጅነት ‹‹ምርምር ለልማት›› በሚል መሪ ቃል ከሚያዚያ 30-ግንቦት 1/2007 ዓ/ም ለ3ኛ ጊዜ በዋናው ግቢ በተካሄደው ሀገር አቀፍ የምርምር አውደ ጥናት ላይ ከ15 ዩኒቨርሲቲዎችና ምርምር ተቋማት በተወጣጡ ጥናት አቅራቢዎች 30 ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል ፡፡
በዩኒቨርሲቲው የምርምር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ፋንታሁን ወልደሰንበት እንደገለጹት አውደ ጥናቱ በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎችና የምርምር ተቋማት ውስጥ የሚሠሩ ተመራማሪዎች በወቅታዊ ችግሮች ላይ የጋራ ግንዛቤ በመያዝ የመፍትሄ አቅጣጫዎችን እንዲጠቁሙ የሚያግዝ ነው፡፡ በተጨማሪም ዓውደ ጥናቱ በዩኒቨርሲቲዎች መካከል የልምድ ልውውጥ በማድረግና የትብብር ምስረታዎችን በማጠናከር ረገድ ሀገራዊ ፋይዳው የጎላ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ጥናታዊ ጹሑፎቻቸውን ካቀረቡት መካከል በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን ትምህርት ክፍል መምህር ሙዑዝ ሃይሉ አንዱ ሲሆኑ የጥናታቸውም ርዕስ “ሀገር አቀፍና አለም አቀፍ ጋዜጦች ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሰጡት ሽፋን” የሚል ነው፡፡ መገናኛ ብዙሃን ከሚዲያ መርሆች አንፃር ግድቡን አስመልክቶ እንዴት እደዘገቡት ማወቅን ዓላማ ያደረገው ጥናት በአንዳንድ ጋዜጦች ላይ የሚወጡ ዘገባዎች የናይል ተፋሰስ አገሮችን ጥቅምና ፍላጎት ማዕከል ያደረጉ ሳይሆኑ በየአገሮቻቸው ፍላጎት ላይ ብቻ ያተኮሩ መሆናቸውን ያሳያል፡፡ ግድቡ ለኢትዮጵያም ሆነ ለጎረቤት ሀገሮች ያለው የልማት ጠቃሚነት የጎላ ስለሆነ ሚዲያዎች ሚዛናዊ ሽፋን መስጠት እንደሚገባቸው በጥናቱ ተጠቁሟል፡፡
በዩኒቨርሲቲው የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ-ጽሑፍ (አማርኛ) ትምህርት ክፍል መምህርት ህሊና ሰብስበው ‹‹የግጭት አፈታት ሥርዓት ክዋኔ በጌዲኦ ብሄር›› በሚል ርዕስ ጥናታዊ ጽሁፍ ያቀረበች ሲሆን የብሄረሰቡ የግጭት አፈታት ሥርዓት ከማህበረሰቡ መልካም እሴቶች ጋር የተቆራኘ መሆኑን እና የማህበረሰቡን የእርስ በእርስ ግንኙነት እንደሚያጠናክር ዳስሳለች፡፡ የጥናት አቅራቢዋ በሰጠቸው ተጨማሪ አስተያየት በአውደጥናቱ የተለያዩ የምርምር ውጤቶች መቅረባቸው ወጣት ተመራማሪዎች ልምድ እንዲቀስሙ ያስችላል ብላለች፡፡
በዩኒቨርሲቲው የአስተዳደር ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝደንት ዶ/ር የቻለ ከበደ ባደረጉት የመዝጊያ ንግግር ዩኒቨርሲቲው በዋናነት ከሚያሳካቸው አበይት ተልዕኮዎች መካከል ማህበረሰብ ተኮር የሆኑ ምርምሮች ማካሄድ አንዱ ስለሆነ ተመሳሳይ የምርምር ስራዎች በቀጣይም በሌሎች ኮሌጆች በተያዘላቸው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አሳውቀዋል፡፡